6 ሐሰተኞቹን ከእውነተኞቹ የትንቢት አገልግሎቶች የምንለይባቸው መንገዶች

ዶ/ር ጆሴፍ ማቴራ

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በማህበራዊ ድህረገፆች በኩል (ከአጥብያ ቤተ-ክርስቲያናት ይልቅ)፣ ለብዙሐን ሣቢ የሆኑ የትንቢት አገልግሎቶችና መንፈሳዊ መሪዎች “ትንቢታዊ አገልግሎትን” በየግል ለመስጠት ቃል በመግባት ተነስተዋል።

ይህ ታድያ በብዙ ደረጃ ያሳስበኛል፣ ምክንያቱም በእነዚህ ኮንፍረንሶች ከሚካፈሉት ሰዎች መካከል አብዛኛዎቹ ጠና ያሉ የቤተ-ክርስቲያን መሪዎች ሳይሆኑ ይልቁንስ ጥልቅ የሆነ የመጽሐፍ ቅዱስ እውቀትና ግንዛቤ የሌላቸው ሕዝቦች መሆናቸው አንዱ ነው።

መጋቢ (ፓስተር) በመሆን ከ1984 ጀምሮ ካሳለፍኩት ህይወት እንደተማርኩት፣ አንድን ቤት በሰዎች ጢም አድርጎ መሙላት የሚቻለው፣ ሁሉም ታዳሚ የየግሉ ትንቢታዊ ቃላትን እደሚደርሰው በሚያስመስል መንፈስ በማገልገል አልያም ደግሞ ነፃ ምግብ በመስጠት ነው። 

ይህ የሩቅ ለቅሶ ከ1940ዎቹ ጀምሮ፣ ትንቢታዊ እንቅስቃሴዎች በሕዝቡ ላይ መንፈሳዊ መነቃቃትን ማምጣት ሲጀምሩና ከሶስት እስከ አምስት ከሚሆኑና እርስ በእርሳቸው መተናነጽና አንዱ ሌላውን መገሠፅ ከሚችሉ የቤተ-ክርስቲያን ሽማግሌዎች በሚዋቀር “ትንቢታዊ አመራር” ውስጥ አባል በሆኑ ሰዎች አገልግሎት ሲቀርብ እንዲሁም በአንድነት ስለ ሕዝቡ ከጌታ ቃል ይመጣ ዘንድ ከሚጸልዩ አባቶች ጋር በመሳተፍ ይካሄድ ነበር።

በአሁን ጊዜ፣ ብዙዎች መጋቢ ወይንም የቤተ-ክርስቲያን ሽማግሌ በሌላቸው ብሎም ሃላፊነትና የመልካም እረኛ እይታ/ቁጥጥር በማይታይባቸው ኮንፍረንሶችና ጉባኤዎች በመካፈል “የግል ቃል” ከአገልጋዮች ለመቀበል ሲሰለፉ ይስተዋላሉ። በእርግጥ ይህ መጋቢዎችና ጠና ያሉ የቤተ-ክርስቲያን መሪዎች እርስበርሳቸው ለመተናነጽ፣ ለመማማርና በትንቢት ለመገልገል ከሚያደርጉት ስብስብ ይለያል። ይሁን እንጂ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ሳይቀር የትንቢት ቃሎች መመዝገብና በሌሎች መሪዎች መዳኘት ትንቢት ተናጋሪውን ነብይ እንዲሁም ትንቢት ተቀባዮቹን ምዕመናን ለመጠበቅ ይጠቅማል። (አንዳንድ ጊዜ፣ ግለሰቦች የተነገረውን የትንቢት ቃል ከአውድ ውጭ በመውሰድ፤ አንድሰው ሊያመለክት ያልፈለገውን ደግሞም ያልተናገረውን መልዕክት ሊያስቡ ብሎም ሊያሰራጩ ይችላሉ።)

በተጨማሪም፣ ትንቢታዊ አገልግሎቶችን በአዲስ ኪዳን ውስጥ ስንመረምር፣ ጳውሎስ በ1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች መልዕክቱ ልንከተለው የሚገባንን መንገድና መመሪያ አስቀምጦልናል። በዚህ አርዕስት ላይ በአዲስ ኪዳን ብዙ ነጥቦችን እናገኛለን።

1. ብዙዎቹ ትንቢቶች ቀላል የትንቢት ስጦታ መገለጫዎች ናቸው። በ1ኛ ቆሮ 14፡3 እንደተጻፈው፣ “ትንቢትን የሚናገር ግን ለማነጽና ለመምከር ለማጽናናትም ለሰው ይናገራል።”

ከዚህ አውድ ሳንወጣ፣ ጳውሎስ እንደተናገረው፤ ሁሉም አማኞች መንፈሳዊ ስጦታን መሻት (14፡1) በይበልጥ ደግሞ ትንቢት መናገርን (14፡1) መፈለግ ይኖርባቸዋል፣ ትንቢትን የሚናገሩ ቤተ-ክርስቲያን ያንጻሉና (14፡4)።

2. ይህ ስጦታ ሁሉ ሊጠማው የሚገባ ቢሆንም እንኳ (ሙሴ ራሱ ሳይቀር እንደጠቀሰው ዘኍ 11፡29)፣ የመጀመሪያ ተቀዳሚ የአገልግሎት ስጦታቸው፣ በኤፌ 4፡11 ላይ እንደተገለጸው የትንቢት አገልግሎት ከሆኑት ነብያት ስጦታ ግን ይለያል።

ይህ ማለት፣ ብዙ ሰዎች በነጻነት መስራት እንደመቻላቸው መጠን (እና በልምምድ ትክክለኛነትን ማዳበር እንደመቻላቸው) በቀላል የትንቢት ስጦታ (እንደ ብዙዎቹ አታላይ እንቅስቃሴዎች)፣ ምንም እንኳ ልምድ፣ የአመራር ብቃት፣ ጸጋ እና በኤፌሶን 4፡11 ላይ እንዳለው የተቀዳሚ ነብይነት ጥሪ ቢጎድላቸውም፣ እራሳቸውን “የነብያት ማኅበር” ብለው ሾመው ይታያሉ።

3. ማኅበር ወይንም የትንቢት አገልግሎት አካልና ተግባር በ1ኛ ቆሮ 14፡3 ልይ እንዳለው ቀላል የትንቢት ስጦታ ባላቸው ሁሉ ሊወሰድ የሚገባ አይደለም፤ ምንም እንኳ ሁሉም ክርስቲያኖች በዝህ ስጦታ ውስጥ እንዲንቀሳቀሱ ቢበረታቱም፣ የኤፌ 4፡11 የትንቢት ስጦታ ለአንድ አንዶች ብቻ፣ በቤተ-ክርስቲያን እና በመስሪያቤት ውስጥ እንዳላቸው ስፍራ የሚሰጥ ነው፤ ከሁለቱ የቃል ክፍሎች እንደምንረዳው።

4. በቤተ-ክርስቲያን በትንቢት አገልግሎት ስጦታ የሚንቀሳቀሱ ሁሉ የተለያዩ መጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች እንደሚጠቁሙት ውጫዊ ምልከታ፣ ክትትልና አስተዳደርን ያካተተ መሰረታዊ አገልግሎት ሊኖራቸው ይገባል። (1ቆሮ 12፡28፣ ኤፌ 2፡20፣ 4፡11፣12 እና ሐዋ 13፡1-2) እንደሚያመለክተው በአንጾኪያ በነበረችው ቤተ-ክርስቲያን የነበሩት ነብያት ራሳቸው የክትትልና ቁጥጥር ማኅበር መስርተው ነበር።

ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ በአንዳንዶቹ ትንቢታዊ ኮንፍረንሶች ግንኙነት የሌላቸው፣ ተጠያቂነትን ያጡ እና ከ አጥቢያ ቤተ-ክርስቲያን የተገነጠሉ ግለሰቦች ሲመሯቸው ይስተዋላል —ከቦታ ቦታ በመንቀሳቀስ ታዳሚዎችን ሰብስቦ “ቃልን” ማምጣት— አማካዮቹ ለጋ አማኞች በትንቢት ከልክ በላይ የሚሳቡበት ትልቁ ምክንያት፣ በቃሉና በመንፈሳዊው አለም የጌታን ድምጽ በራሳቸው ለመለየት የሚያስፈልገው ብስለት ስለሚጎድላቸው ነው።

ስለዚህ፣ አንድ ሰው “ትንቢታዊ ኮንፍረንስ” በተባለ ስፍራ ከመሄዱ በፊት፣ በቅድምያ “የትንቢት ሰዎቹ” ከየትኛው ቡድን እንደሚመደቡ፣ የትንኛዋ ቤተ-ክርስቲያን አባል እንደሆኑ፣ በአጥብያ ቤተ-ክርስቲያን በየትኛው አስተዳደራዊ እርከን እንደሚያገለግሉና ለማን ተጠያቂነት እንዳለባቸው ወይንም ማን እንደሚከታተላቸው መጠየቅ ያስፈልጋል። የእንዚህን መሰረታዊ ጥያቄዎች ምላሽ ሳይገኝ አገልግሎቶቹን ሄዶ መካፈል፣ ጅልነት (ብሎም አንዳንዴ አደገኛ ነው።) በተጨማሪም በአጥብያ ቤተ-ክርስቲያናቹ ለማረም እና የተነገረውን ቃል ለመተርጎምና እንዲፈጸም ለመርዳት በቦታቸው ከተገኙ ሽማግሌዎች፣ መጋቢዎችና መሪዎች ውጭ ትንቢታዊ አገልግሎትን መቀበል አለማስተዋል ነው።

5. በጳውሎስ መልዕክት አውድ ውስጥ በ 1ኛ ቆሮንጦስ 14፣ ትንቢት ሰዎች ከአጥብያ ቤተ-ክርስቲያናቸው ይለዩ ዘንድ ሳይሆን ቤተ-ክርስቲያን ትታነጽ ዘንድ ይሰጣል። በተጨማሪም፣ ቀላል የትንቢት ስጦታ አነስ ባለ ቡድን ወይንም በቤተ-ክርስቲያን ስብስብ ውስጥ በይበልጥ ይሰራል። ለዚህ ዋነኛው ምክንያት ደግሞ፣ በቤተ-ክርስቲያን የሚሰጡት የትንቢት አገልግሎቶች በአታላይ ኮንፍረንሶች ከሚሰጠት በበለጠ ተዐማኒነት ይሰጣል ምክኛቱም በሌሎች መሪዎችና ነብያት ይገሠፃሉና ነው (14፡29)

በርግጥ ይህ ከትንቢታ የወንጌል ስራ ማለትም ኢየሱስ መልካሙን ዜና ለሌሎች በምድር በማብሰር ባገለገለው አገልግሎት ከተጠቀመው መንገድ፣ በእጅጉ ይለያል። 

እርሱ አብዛኛውን ግዜ በአለም እውቀትና ጥበብ መንፈሳዊ ስጦታ ውስጥ ይመላለስ ነበር (1ቆሮ 12፡4-8) ይህም አገልግሎቱን ለመጀመሪያ ግዜ በተካፈሉት ሰዎች እይታ ተዐማኒንት እንዲኖረው አድርጎታል (ዮሐ 1፡46-49 እና ዮሐ 4:16-19 ተመልከቱ)።

ለመንገደኛ ወይንም ቤተ-ክርስቲያን ሄዶ ማያውቅ ሰው በአየር መንገድ ተገናኝተን ስንሰብክ፣ በመንገድ ላይ ወይንም ጂም ውስጥ ስንሰራ፣ ኢየሱስ እንዳደረገው (ከቤተ-ክርስቲያን አገልግሎት ውጭ) የትንቢት ስጦታዎችን ማንቀሳቀስ እንዲሁም የሚመለከተውን፣ ሁሉ አዋቂ የሆነውን እና እነርሱንም የሚወዳቸውን የእግዚአብሔርን እውነታ ለሰዎች መግለጥ ምንም ክፋት የለውም።

ይህን ተከትሎ፣ ከትክክለኛ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ደንቦች መካከል ለድኅነት በሚሆን ትንቢታዊ የወንጌል ስራ ወይንም ዳግመኛ ላናያቸው በምንችል መንገደኞች መታነጽ (እናንተ ይተዋወቃችኋቸው፣ በተመሳሳይ አማኞች እንኳ ሊሆኑ የሚችሉ፣ በማያውቁት ሰው በኩል እግዚአብሔር ለነርሱ ያለውን ፍቅር ለማሳየት እንደ ምልክት የላከውን የሚያበረታታ የትንቢት ቃል የሚያስፈልጋቸው) እና በቤተ-ክርስቲያን ውስጥ ትንቢትን በመጠቀም በሚደረግ የግለሰቦችን ማነጽና ማስታጠቅ መካከል ያለውን ልዩነት ጠንቅቆ መማር ያስፈልገናል።

6. በጳውሎስ በኩል በተሰጠን መመሪያ ላይ መንፈሳዊ ስጦታዎችን እንዴት መጠቀም እንዳለብን በ 1ኛ ወደ ቆሮንጦስ ሰዎች ምዕራፍ 12፣ 13ና 14 እንዲሁም ወደ ኤፌሶን ሰዎች 4፡11-16 እንደሚያመለክተው፣ ሁሉም መንፈሳዊ ስጦታዎች የተሰጡት ለቤተ-ክርስቲያን መታነጽ ነው። ስጦታ፣ እንዲያው ዝም ተብሎ ግለሰብን ለማስደሰት በሚል ምክንያትን እና ለግል ሙላትና ስኬት አይሰጥም። ስለዚህ፣ ይሄ የነብያት የግለኝነት አመለካከት ከመጽሐፍ ቅዱስ አስተምሮ ጋር ከቶ በአንድ ላይ የሚሄድ ሳይሆን፣ በጠንካራው የአሜሪካ የግለኝነት ክርስትና የተገነባና የግልን ጥማት ከክርስቶስ አካልና ህልውና በላይ ከፍ ሊያደርግ ይሚሻ መንፈስ ነው።

በተጨማሪም፣ “የግል ትንቢት” የሚባል ነገር የለም፣ ሁሉም በብሉይም ሆነ በአዲስ ኪዳን ለግለሰብ የተነገሩት ትንቢቶች በሙሉ እንደ ቅርንጫፍ ተከፋፍለው ለእስራኤል መንግስት ስር አልያም ደግሞ ወንጌልን በአጥብያ ቤተ-ክርስቲያን በኩል በይበልጥ ለማስፋፋት መሚሰራው ስራ ውስጥ ይገባሉ።ይሄ ጽሑፍ ቀላል የትንቢት ስጦታን ተጠቅመው ህዝቡን ያጎሩ፣ ተጽዕኖ የፈጠሩ፣ እንዲሁም ባንዳንድ ሁኔታዎች ለገንዘብ ጥቅም ያዋሉትን ሁሉ ፍጹም እንዲወቅሳቸው ጸልያለው። በጎቹ ከመስመር እንዳይወጡ፣ እንዳይበታተኑና ከአካሉ ማለትም ከቤተ-ክርስቲያን እንዳይለዩ እንዲሁም ለመጋቢዎች የክርስቶስ ተከታዮችን በክትትላቸው ስር ሆነው እንዲረዷቸው፣ እንዲያስታጥቋቸውና እንዲያበቋቸው ይጠቅም ዘንድ እጸልያለው።

Download Here

Please follow and like us:

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

ማሕደር

Language
WordPress Image Lightbox